ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በጉራጌ ዞን ጉመር ወረዳ በሚገኘው የአረቅጥ ሐይቅ የዓሳ ሀብትን ለማሳደግ የሚያስችል ዘርፈ ብዙ ተግባራትን በማከናወን ላይ መሆኑ ተገለጸ፡፡
ዩኒቨርሲቲው በአረቅጥ ሀይቅ ላይ የሚያደርገውን ምርምርን መሰረት ያደረገ የማህበረሰብ አገልግሎት ፕሮጀክት አካል የሆነውን ተፈላጊ የሆኑ የዓሳ ዝርያዎችን ዓሳ ከሚያለሙ የሀገሪቱ ቦታዎች በማስመጣት ሀይቁ ላይ ዓሳን የማልማትን ስራን አጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን በዚህም ረገድ የአረቅጥ ሐይቅ የዓሳ ሀብትን ለማሳደግ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን በማከናወን ላይ መሆኑ ተገለጿል፡፡
ዩኒቨርሲቲው የአረቅጥ ሐይቅ የዓሳ ሀብትን ለማሳደግ እያከናወናቸው የሚገኙት የምርምር ስራዎችን እና የማህበረሰብ አገልግሎትን የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች፣ የዓሳ ሀብት ተመራማሪዎች እና የአረቅጥ ከተማ ከፍተኛ አመራሮች ጎብኝተዋል፡፡ በጉብኝቱም ወቅት የተገኙት የወልቂጤ ዩኒቨርስቲ የምርምር እና የቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዝደንት የሆኑት ዶ/ር ዮሃንስ ገብሩ እንደገለጹት ዩኒቨርሲቲው የዓሳ ሀብትን ለማሳደግ እያከናወናቸው የሚገኙት የምርምር ስራዎች የሚበረታቱ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ የዓሳ ልማትን ለማሳደግ እየተደረገ ያለው ጥረትም ተስፋ ሰጭ መሆኑን የገለጹት ምክትል ፕሬዝዳንቱ በቀጣይ ስራው በስፋት በዞን ውስጥ በሚገኙት የውሃ አካላት እና ለአርሶ አደሩ እንዲደርስ ከፍተኛ የሆነ ርብርብ ማድረግ ይገባል ብለዋል፡፡
በስፍራው ተገኝተው ሀሳባቸውን የሰጡት የአረቅጥ ከተማ ምክትል ከንቲባና የኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪ የሆኑት አቶ ይድነቃቸው በበኩላቸው እንደገለጹት ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በአረቅጥ ሐይቅ ላይ እያደረገ ያለውን መልካም ስራ አድንቀው ስራው የበለጠ እንዲሰፋ እና የአካባቢው ማህበረሰብ ከዘርፉ ተጠቃሚ እንዲሆን ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በመቀናጀት የድርሻችንን አስተዋጽኦ እናበረክታለን ሲሉ ተናግረዋል፡፡
በስራ ጉብኝቱ ወቅት በዘርፉ የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች የሆኑት ዶ/ር ይርጋ እናውጋው የዓሣ ሀብት እና የውሃ ሳይንስ መምህርና ተመራማሪ እና ዶር ሰለሞን ዋጋው የዓሳ፣ አኳካልቸርና የውሃ ሳይንስ መምህርና ተመራማሪ በአረቅጥ ሐይቅ እየተከናወኑ ስለሚገኙ የምርምር ስራዎች እና የማህበረሰብ አገልግሎት ተግባራት ለወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ እና ለአረቅጥ ከተማ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ሰፊ ገለጻ አድርገውላቸዋል፡፡
በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የዓሣ ሀብት እና የውሃ አካላት ተመራማሪ የሆኑት ዶ/ር ይርጋ እናውጋው እንደገለጹት የአረቅጥ ሐይቅን ጨምሮ በጉራጌ ዞን ለዓሣ እርባታ ምቹ የሆኑ ሐይቆችና ግድቦች ቢኖሩም ምርቱን በሚፈለገው ደረጃ ማሳደግ አልተቻለም። ለዚህም እንደምክንያት የሚያነሱት የዓሳ ጫጩት አቅርቦት፣ ዘመናዊ ማስገሪያ መሳሪያዎች አቅርቦት እጥረት፣ የገበያ ትስስር እና የማጓጓዣ ተግዳሮቶች መሆናቸውን አመልክተዋል፡፡
ዶ/ር ሰለሞን ዋጋው በበኩላቸው ያሉትን ችግሮች በመፍታት የጉራጌ ዞን የዓሳ ሀብት ምርቱን በሚፈለገው ደረጃ ለማሳደግ እየተሠራ እንደሚገኝ ገልጸው፤ የዓሳ ጫጩቶችን ከሰበታ የዓሳ እና ሌሎች የውሃ አካላት የምርምር ተቋም የማምጣት እና የማሰራጨት ስራዎችን የማጠናከር ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ አስታውቀዋል፡፡ በዚህም መሰረት ከሰበታ የዓሳ ምርምር ማዕከል የቆሮሶ ዓሳ ጫጩቶችን በማምጣት በአረቅጥ ሐይቅ የማስገባት ስራ መከናወኑን ገልፀው በቀጣይም የዓሳ ሀብቱን ለማሳደግ እንደ ተመራማሪ ተመሳሳይ ስራዎች ያለማቋረጥ የሚሰሩ መሆኑን ገልፀዋል።
ዶ/ር ይርጋ እናውጋው እና ዶ/ር ሰለሞን ዋጋው አያይዘውም እንደገለጹት የዓሣ ግብርና የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ፣ ገቢ ለማመንጨት የሚያስችል እና ለወጣቶች የሥራ ዕድልን ከመፍጠር አንጻር ዩኒቨርሲቲው ከዞኑ ጋር በመተባበር ተከታታይነት ያላቸውን ስራዎችን ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።
የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክተር የሆኑት ቸርነት ዘርጋ በበኩላቸው እንደገለጹት የዞኑን ዓሣ ሀብት ከመጠበቅ እና የምርት መጠኑን ለማሳደግ የዓሳ ጫጩቶችን በዞኑ ከሚገኙ የውሃ አካላት እንዲገቡ አስፈላጊው እገዛ እየተደረገ እንደሆነ በመግለፅ የዞኑ የዓሳ ሀብት ባለሞያዎች እና አስጋሪዎችም በሕጋዊ፣ በዘመናዊ እና ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ እንዲያጠምዱ እና የዓሳ ሀብቱን ከመጠበቅ አንፃር ግንዛቤ እና ተግባራዊ ስልጠና እንዲሰጣቸው በመደረግ ላይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በመጨረሻም ዶ/ር ዮሀንስ ገብሩ ለማህበረሰቡ ጠቃሚ የሆኑ እንደዚህ ዓይነት ስራዎች ወደፊት በስፋት እንደሚሰሩ ገልፀው ይህ ስራ ከጅምሩ ጀምሮ በባለቤትነት እያከናወኑ ላሉት የዩኒቨርሲቲያችን መምህራንና እና ተመራማሪዎች እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላትን አመስግነዋል።
ለጥበብ እንተጋለን!
We Strive for Wisdom!
የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የህዝብና ዓለምአቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት